በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

ረሃብ በአፍሪካ

በቦረና ድርቅ ከትምህርት ያስታጎላቸው ከ2ሺሕ800 በላይ ተማሪዎች አልተመለሱም
please wait

No media source currently available

0:00 0:05:14 0:00

ላለፉት ሦስት ዓመታት፣ በቦረና ዞን በተከሠተው ተከታታይ ድርቅ፣ ትምህርታቸውን ከአቋረጡ ተማሪዎች ከ2ሺሕ800 በላይ የኾኑቱ፣ ወደ ትምህርት ገበታቸው እንዳልተመለሱ፣ የዞኑ ትምህርት ጽሕፈት ቤት አስታወቀ።

የቦረና ዞን ትምህርት ጽሕፈት ቤት ሓላፊ አቶ ተስፋዬ ወልደ ሚካኤል፣ ድርቁ በርትቶ በነበረባቸው ወራት፣ ትምህርት ከአቋረጡ ከ7ሺሕ800 በላይ ተማሪዎች ወደ አራት ሺሕ ገደማዎቹ፣ ወደ ትምህርት ገበታ ሲመለሱ የተቀሩት ግን፣ በጋብቻ እና ሌሎች ተጓዳኝ እክሎች ሳይመለሱ መቅረታቸውን አስረድተዋል።

የቦረና ዞን 12ኛ ክፍል ተማሪዎች፣ ለዘንድሮው መልቀቂያ ፈተና በአግባቡ እንዳይዘጋጁ፣ ድርቁ ዕንቅፋት እንደፈጠረባቸውም ተናግረዋል፡፡

በቦረና ዞን፣ ከቅርብ ወራት ወዲህ የጣለው ዝናም፣ አካባቢው በልምላሜ እንዲሸፈን ቢያደርግም፣ ነዋሪዎች ላለፉት ሦስት ዓመታት በርትቶ ከሰነበተው ድርቅ ጫና አሁንም አልተላቀቀም። የዞኑን ኢኮኖሚ ክፉኛ ያዳከመው ተከታታይ ድርቅ፣ በመማር ማስተማር ሒደቱ ላይ ያደረሰው አሉታዊ ጫና ከባድ እንደኾነ፣ የቦረና ዞን ትምህርት ጽሕፈት ቤት ሓላፊ አቶ ተስፋዬ ወልደ ሚካኤል ተናግረዋል።

“ባለፉት ዓመታት፣ ለአምስት ተከታታይ የዝናም ወቅቶች፣ ዝናም አልዘነመም ነበር፡፡ ከዚኽም የተነሣ ተማሪዎች ከትምህርት ገበታ ቀርተዋል። በተለይ በትምህርት ቤቶች፣ የመጠጥ ውኃ ችግር ነበረ። ከዚኽም የተነሣ፣ በመጀመርያው መንፈቀ ዓመት፣ ከ7ሺሕ800 መቶ በላይ ተማሪዎች ትምህርታቸውን አቋረጡ። በዚኽ ወቅት፣ በትምህርት ቤቶች የምገባ መርሐ ግብር በፍጥነት ተጀመረ፡፡ ይኹንና፣ ትምህርታቸውን ከአቋረጡ ከ7ሺሕ800 ተማሪዎች መካከል፣ በሕመም፣ በጋብቻ እና በረኀብ፣ 2ሺሕ869 ተማሪዎች ወደ ተማሪ ቤት አልተመለሱም፤ የተቀሩት ግን ወደ ትምህርት ገበታቸው ተመልሰው በመማር ላይ ናቸው።”

ዘንድሮ፣ የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ መልቀቂያ ፈተና ተፈታኙ፣ ሃለኬ ሞሉ ፤ “በፊት በድርቁ ምክንያት፣ ተማሪው በትምህርት ቤት ተገኝቶ ትምህርቱን ለመከታተል አልቻለም፡፡ ያ ኹኔታ በጣም ጎድቶናል። ያለን አማራጭ ትምህርት ብቻ በመኾኑ፣ ለሁለት እና ለሦስት ቀናት ያለምግብ እየቆየንም ቢኾን፣ እርስ በርሳችን እየተደጋገፍን እዚኽ ደርሰናል።’ ይላል።

ደኪ በንት ስላሳለፈችው ጊዜ ስትናገር፤ “የድርቁ ጫና በጣም ከባድ ነው፤ ምክንያቱም እኛን የሚያስተምሩን ቤተሰቦቻችን ናቸው፤ ቤተሰቦቻችን ሀብታቸው ከእጃቸው ካለቀ የምንማርበት አይኖረንም፡፡ በተጨማሪም፣ ቤተሰቦችኽ እየተቸገሩ በክፍል ውስጥ ኾነህ ትምህርት መከታተል በጣም ከባድ ነው።” ብላለች።

በተለይ ከገጠር ቀበሌዎች ወደ ከተማ መጥተው፣ ቤት ተከራይተው ትምህርታቸውን የሚከተታተሉ ተማሪዎች፣ እንዲሁም በዞኑ በተለያዩ ወረዳዎች ተገንብተው ባሉ የተማሪዎች ማደርያዎች ወይም(ሆስቴሎች) ያሉ ተማሪዎች የድጋፍ እጥረት እንዳሉባቸው ይናገራሉ።

በያበሎ በሚገኘው የሻለቃ ጃታኒ አሊ ታንዱ መታሰብያ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት መምህር ዳንኤል አኖ፣ “ዘንድሮ የ12ኛ ክፍል መልቀቂያ ፈተና ለሚወስዱ ተማሪዎቻችን፣ አጋዥ ወይም የማጠናከሪያ ሥልጠና(Tutorial Class) እየሰጠን ነን፡፡ የልጆቹን ስኬት የሚወዱ፣ ከዐቃቤ ሕግ ጽሕፈት ቤት እና ከቦረና ዩኒቨርሲቲ መምህራን፣ በዚኽ የማስተማር ሥራ እየተሳተፉ ነው፡፡” ይላሉ።

የትምህርት ቤቱ ርእሰ መምህር አቶ ዋቆ ኩራ፣ ተማሪዎቹ ለዝግጅት ያላቸው ጊዜ አጭር ቢኾንም፣ እያስመዘገቡ ያሉት የክፍል ውጤት መልካም መኾኑን ይናገራሉ።

በዚኽ ትምህርት ቤት፣ ትልቁን አማካይ ውጤት ያስመዘገበው የ12ኛ ክፍል ተማሪ፣ መለኪያችን ስኩል ማኔጅመንት ኢንፎርሜሽን ሲስተም ነው፡፡ ተማሪዎቻችንን፣ ይህ ሁሉ ጫና ቢደርስባቸውም፣ አንድ የ12ኛ ክፍል ተማሪ፣ ይህን ውጤት ማስመዝገቡ ተስፋ እንዳንቆርጥ ያደርገናል።”

“በዚኽ ትምህርት ቤት፣ ትልቁን አማካይ ውጤት ያስመዘገበው የ12ኛ ክፍል ተማሪ፣ መለኪያችን ስኩል ማኔጅመንት ኢንፎርሜሽን ሲስተም ነው፡፡ ተማሪዎቻችንን፣ ይህ ሁሉ ጫና ቢደርስባቸውም፣ አንድ የ12ኛ ክፍል ተማሪ፣ ይህን ውጤት ማስመዝገቡ ተስፋ እንዳንቆርጥ ያደርገናል።”

የቦረና ዞን ትምህርት ቢሮ ሓላፊ አቶ ተስፋዬ ወልደ ሚካኤል፣ መንግሥት፣ አሁንም ተማሪዎችን በምገባ መርሐ ግብር ድጋፍ እየሰጣቸው እንደኾነ አስረድተዋል።

“ተማሪዎቹ ከትምህርት ገበታቸው እንዳይስተጓጎሉ፣ በመጀመርያ ደረጃ፣ ምግብ ማቅረብ ያስፈልጋል። በዞኑ ካሉ 483 ትምህርት ቤቶች፣ በ111ዱ፣ በተባበሩት መንግሥታት የዓለም የምግብ ፕሮግራም፣ ርዳታ በመድረስ ላይ ነው፤ በተቀሩት 307 ትምህርት ቤቶች ላይ፣ መንግሥት በራሱ በጀት ምግብ እያቀረበ ነው። ይህም በኦሮሚያ ትምህርት ቢሮ በኩል በጀት ተይዞ፣ ግልጽ ጨረታ ወጥቶ፣ ገዳ ዩኒየን አሸንፎ አሁን ተማሪዎች ምግብ እያገኙ ናቸው።”

የውኃ እጥረቱን አስመልክቶ፣ የዞኑ መጠጥ ውኃ ጽሕፈት ቤት፣ በቦቴ ውኃ ለትምህርት ቤቶች እያቀረበ እንደኾነ አቶ ተስፋዬ ገልጸዋል፡፡ በቦረና የተለያዩ ወረዳዎች ተገንብተው አገልግሎት በመስጠት ላይ ያሉት የተማሪ ማደርያዎች(ሆስቴሎች)፣ በቁጥር በርከት ያሉ ተማሪዎችን እያስጠለሉ በመኾኑ፣ ወደፊት ሆስቴሎቹን የማስፋፋቱ መርሐ ግብር እንደሚቀጥል፣ የዞኑ የትምህርት ቢሮ ሓላፊ አቶ ተስፋዬ ወልደ ሚካኤል አመልክተዋል።

የጎፋ ዞን የጎርፍ ተጠቂዎች ወደ ቀዬአቸው ለመመለስ ድጋፍ ጠየቁ
please wait

No media source currently available

0:00 0:04:56 0:00

በደቡብ ክልል ጎፋ ዞን ኡባ ደብረ ፀሐይ ወረዳ በደረሰው የጎርፍ አደጋ የተፈናቀሉ ሰዎች፣ ወደ ቀዬአቸው ለመመለስ ድጋፍ ጠየቁ። የጎፋ ዞን አስተዳደር የአደጋ ስጋት ሥራ አመራር፣ የተፈናቀሉ ዜጎችን መልሶ ለማቋቋም፣ ከ158 ሚሊዮን ብር በላይ እንደሚያስፈልግ አስታውቋል።

የኡባ ደብረ ፀሐይ ወረዳ አስተዳዳሪ በበኩላቸው፣ የተፈናቀሉ ዜጎችን መልሶ ለማቋቋም፣ ከክልሉ ቀይ መስቀል እና ከአደጋ ስጋት ሥራ አመራር ጋራ በመተባበር፥ ቁሳቁሶች እየተሰባሰቡ፣ በጎርፍ የተጥለቀለቀው እየተጠረገ፣ የጎርፍ መውረጃው እየተጠለፈ እንደሚገኝ ተናግረዋል።

የአሜሪካ ድምፅ በስልክ ያነጋገራቸውና ጎርፍ ያፈናቀላቸው አቶ አብርሃም ዘኬዎስ፤ ቤታቸው በጎርፍ ተጠራርጎ በመወሰዱ መጠለያ አልባ መኾናቸውን ይናገራሉ። ቤታቸው ተሠርቶ ወደ ቀዬአቸው መመለሱን አብዝተው የሚፈልጉት ነገር እንደኾነ አመልክተዋል።

የስምንት ልጆች እናት መኾናቸውን የተናገሩት ሌላዋ አስተያየት ሰጪ ወይዘሮ ዙፋን ታደሰም፣ ከአቶ አብርሃም ዘኬዎስ ጋራ ተመሳሳይ ጥያቄ አላቸው፡፡

የኡባ ደብረ ፀሐይ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ኢልቶ ኢፀና፣ የተፈናቀሉ ዜጎችን መልሶ ለማቋቋም፣ ከክልሉ ቀይ መስቀል እና ከአደጋ ስጋት ሥራ አመራር ጋራ በመተባበር ጥረት እየተደረገ መኾኑን ገልጸዋል።

ቤት ለመሥራት የሚረዱ ቁሳቁሶችን የመሰብሰብ፣ በጎርፍ የተጥለቀለቀውን የመጥረግ፣ የጎርፍ መውረጃውን የመጥለፍ ሥራ መጀመሩን፣ አቶ ኢልቶ ጨምረው ተናግረዋል።

የዞኑ የአደጋ ስጋት ሥራ አመራር ጽሕፈት ቤት ሓላፊ አቶ ማርቆስ መሰለ፣ የተፈናቀሉ ዜጎችን መልሶ ለማቋቋም፣ 158 ሚሊዮን 669ሺሕ 609 ብር እንደሚያስፈልግ ይናገራሉ።

አቶ ማርቆስ፣ 124 ሚሊዮን 226ሺሕ 244 የግለሰቦች ሀብት፤ ከ34 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመቱ መሠረተ ልማቶች እና ማኅበራዊ ተቋማት መውደማቸውን አስታውቀዋል።

እንደ አቶ አብርሃም ያሉ ጎርፍ ያፈናቀላቸው ነዋሪዎች፥ ተጠልልው በሚገኙባቸው ትምህርት ቤቶች፣ ቤተ ክርስቲያንና ጤና ጣቢያ የሚደረግላቸውን ሰብአዊ ድጋፍ አድንቀው፤ በዚኽ መልኩ ግን መቀጠል ስለማይቻል፣ ለዘላቂ መፍትሔ ትኩረት እንዲሰጥ አበክረው ጠይቀዋል።

በአደጋው ለተጎዱት ነዋሪዎች፥ ከጋሞ፣ ከኮንሶ፣ ከደቡብ ኦሞ፣ ከማሌ ወረዳ እና ሌሎች አጎራባች ዞኖች እና ከክልል ቢሮዎች፣ እንዲሁም ከደቡብ ክልል ቀይ መስቀል ማኅበር፣ ሰብአዊ ድጋፍ እየቀረበላቸው እንደሚገኝ ገልጸዋል።

በኡባ ደብረ ፀሐይ ወረዳ የጎርፍ አደጋ፥ 21 ሰዎች ሲሞቱ፣ 17 ሰዎች ከባድ፣ 89 ሰዎች ደግሞ ቀላል የአካል ጉዳት እንደረሰባቸው ያስታወሱት አቶ ማርቆስ፣ ወረዳው በውል በአደረገው ማጣራት፣ የተፈናቀሉ ሰዎች ቁጥር ከ5ሺሕ ወደ 2ሺሕ167 መቀነሱን አስታውቀዋል። በዚኹ ማጣራት፣ 217 ቤቶች በጎርፉ የተወሰዱ ሲኾን፣ ከ3ሺሕ500 በላይ የቤት እንስሳት መሞታቸው ተረጋግጧል።

ተጨማሪ ይጫኑ

XS
SM
MD
LG