በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

ረሃብ በአፍሪካ

የርዳታ እህል ለተረጂ ያልደረሰው “በመጠነ ሰፊና የተቀናጀ ዘመቻ” እንደኾነ ዩኤስኤአይዲ አስታወቀ
please wait

No media source currently available

0:00 0:04:08 0:00

ዩናይትድ ስቴትስ ለኢትዮጵያ የምትለግሰው የምግብ ርዳታ እንዲቋረጥ ያደረገችው፣ “ለተረጂው አይደርስም” በማለት እንደኾነ በይፋ አስታወቀች፡፡ የዩናይትድ ስቴትስ ዓለም አቀፍ የልማት ተራድኦ ድርጅት (USAID)፣ ለኢትዮጵያ የሚሰጠው የምግብ ርዳታ፣ “ለተረጂዎች አይደርስም” ሲል፣ ርዳታውን ማቋረጡን፣ በዛሬው ዕለት ይፋ አድርጓል።

“ለተቸገረው የኢትዮጵያ ሕዝብ መድረስ የሚገባው የምግብ ርዳታ፣ ወደ ሌላ አቅጣጫ እንዲቀየስ የሚያደርግ፣ መጠነ ሰፊ እና የተቀናጀ ዘመቻ መኖሩን”፣ ዩኤስኤአይዲ እና የኢትዮጵያ መንግሥት በመተባበር ባደረጉት ማጣራት ከድምዳሜ ላይ መድረሳቸውን፣ የድርጅቱ ቃል አቀባይ በይፋ በሰጡት መግለጫ አብራርተዋል።

ኾኖም፣ ርዳታው ለተረጂ ወገኖች እንዳይደርስ ከሚደረገው ዘመቻ ጀርባ ያለው ማን እንደኾነ፣ በመግለጫው ተለይቶ አልጠቀሰም። ዩናይትድ ስቴትስ፣ የአፍሪካ ቀንድንና አካባቢውን ክፉኛ ከጎዳው ድርቅ እና በቅርቡ ከአበቃው የሰሜን ኢትዮጵያው ጦርነት ጋራ በተያያዘ፣ ለርዳታ ጠባቂነት የተጋለጡትን ጨምሮ፣ ቁጥሩ 20 ሚልዮን ለሚደርሰው ተረጂ ሕዝብ ዋናዋ ለጋሽ ሃገር ናት።

ሮይተርስ የዜና ወኪል በተመለከተው እና በተለይ ኢትዮጵያ ውስጥ፣ የረድኤት ሥራ ለሚያከናውኑ የውጭ ለጋሽ ቡድኖች የቀረበ አንድ ሰነድ፣ “የርዳታ ምግቡ፥ ለአገሪቱ ልዩ ልዩ ወታደራዊ ክፍሎች እንዲሰጥ ተደርጓል፤” ብሎ፣ ዩኤስኤአይዲ እንደሚያምን ይጠቁማል።

ርዳታውን ከታለመለት ዓላማ ውጭ የማዋሉ ድርጊት፣ “በፌዴራል እና በክልል መንግሥታት አካላት የተቀነባበረ ዘመቻ፣ በመላ አገሪቱ የሚገኙ ወታደራዊ ክፍሎች፣ ለሰብአዊ ርዳታ የመጣው ምግብ ተጠቃሚ ናቸው፤” ሲል፣ ዩኤስኤአይዲ’ን ያካተተው ይኸው የለጋሾች ቡድን ሰነድ አመልክቷል።

የኢትዮጵያ መንግሥት እና የመከላከያ ሠራዊቱ ቃል አቀባዮች፣ ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ለጊዜው አፋጣኝ ምላሽ አልሰጡም። ዩኤስኤአይዲ’ም በበኩሉ፣ ሪፖርቱን በተመለከተ ተጨማሪ ማብራሪያ ከመስጠት ተቆጥቧል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ፣ የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንተኒ ብሊንከን፣ በሳዑዲ አረቢያ እየተካሔደ ካለው ጉባኤ በትይዩ፣ ዛሬ ኀሙስ፣ ከኢትዮጵያው ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኰንን ጋራ በጉዳዩ ዙሪያ ተወያይተዋል።

የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት፣ የሁለቱን ባለሥልጣናት ውይይት ተከትሎ ባወጣው መግለጫ፣ የኢትዮጵያ መንግሥት፣ በጉዳዩ ላይ ሙሉ ምርመራ ለማካሔድ፣ ከዩናይትድ ስቴትስ ጋራ ተባብሮ ለመሥራት የገባውን ቃል፣ ብሊንከን በአዎንታ መቀበላቸውን አመልክቷል።

በተያያዘም፣ የርዳታ ምግብ እደላ ሥርዐቱ አመኔታ ሊጣልበት እንደሚችል እንደታመነ፣ የሥርጭት ሥራውን ለማስቀጠል ድርጅታቸው የሚያቅድ መኾኑን፣ የዩኤስኤአይዲ’ው ቃል አቀባይ ጨምረው አመልክተዋል።

ዩኤስኤአይዲ እና የዓለም የምግብ ፕሮግራም(WFP)፣ በትግራይ ክልል፣ ከፍተኛ መጠን ያለው የምግብ ርዳታ፣ ከታለመለት ዓላማ ውጭ እንዲውል መደረጉን የሚያሳይ መረጃ ከእጃቸው መግባቱን ተከትሎ፣ ካለፈው ወር አንሥቶ በክልሉ ያደርጉት የነበረውን የምግብ እደላ ማቋረጣቸው ይታወሳል።

በትግራይ ክልል፣ በፌዴራል መንግሥት እና በህወሓት ኃይሎች መካከል፣ ለሁለት ዓመታት የዘለቀው እና አያሌ ሺሕዎች ያለቁበት፣ እንዲሁም በ100ሺሕዎች የሚቆጠሩ ዜጎች ለቸነፈር መሰል የረኀብ አደጋ እንዲጋለጡ ምክንያት የኾነው ጦርነት፣ ባለፈው ጥቅምት ወር፣ በደቡብ አፍሪካ - ፕሪቶርያ በተደረሰው የሰላም ስምምነት ማብቃቱ ይታወቃል።

ዩኤስኤአይዲ፣ እ.አ.አ በ2022 የበጀት ዓመት፣ 1ነጥብ5 ቢሊዮን ዶላር የሚጠጋ ዋጋ ያለው ሰብአዊ ርዳታ ለኢትዮጵያ ሰጥቷል። ከዚኽም ውስጥ የሚበዛው፣ በምግብ ርዳታ መልክ የተሰጠ ነው።

ይህ በእንዲህ እንዳለ፣ ትላንት ረቡዕ፣ በለጋሽ ድርጅቶች መካከል የተሠራጨው የቡድኑ ሰነድ፣ ለጋሾች የሚሰጡትን ርዳታ፣ የገንዘብ ማስተላለፊያ ዘዴዎችን በመሳሰሉ “አማራጭ ዘዴዎች” ለተረጂው ወገን ማድረስ ይችሉ ዘንድ፣ የኢትዮጵያ መንግሥት እንዲፈቅድ ይመክራል።

ሰነዱ አክሎም፣ የኢትዮጵያ መንግሥት፥ ድርጊቱን በማውገዝ እና የርዳታ ሠራተኞች እንግልት እንዳይደርስባቸው በመጠየቅ፣ ግልጽ መግለጫ እንዲያወጣ፣ ለጋሾች ጥሪ እንዲያቀርቡ ያሳስባል።

በተመሳሳይ፣ የዓለም ምግብ ፕሮግራም በበኩሉ፣ በመላው ኢትዮጵያ “በተቀነባበረ መንገድ” ይፈጸማል ያለውን የርዳታ ምግብ ከታለመበት ዓላማ ውጭ የማዋል ድርጊት እየመረመረ እንደኾነ፣ ባለፈው ሳምንት የድርጅቱ ምክትል ዲሬክተር፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ለሚያገለግሉ ሠራተኞቻቸው የጻፉት የኢሜል መልዕክት ጠቁሟል። ይኹንና፣ ይህን ተንተርሶ ለቀረበለት ጥያቄ፣ ተቋሙ፣ እስከ አሁን የሰጠው ተጨማሪ ማብራሪያ የለም፡፡

ባለፈው የቦረና ድርቅ ዓመታት ከ3 ሚሊዮን በላይ የቤት እንስሳት ሞተዋል
please wait

No media source currently available

0:00 0:05:19 0:00

በቦረና ዞን ለተከታታይ ሦስት ዓመታት በቆየው ድርቅ፣ ከ3ነጥብ3 ሚሊዮን በላይ የቤት እንስሳት መሞታቸውን፣ የዞኑ የግብርና እና የእንስሳት ሀብት ጽሕፈት ቤት ገለጸ።

የዞኑ ጽሕፈት ቤት ምክትል ሓላፊ ዶክተር ቃሲም ግዩ፣ ለአምስት ተከታታይ የዝናም ወቅቶች በጸናው ድርቅ፣ 46 በመቶ የዞኑ የእንስሳት ሀብት መጥፋቱን፣ ለአሜሪካ ድምፅ ገልጸዋል።

አሁን የድርቁ ወቅት ያለፈ ቢኾንም፣ ነዋሪዎች በበኩላቸው፣ የወደፊት ኑሯቸው እንደሚያሳስባቸው ስጋታቸውን አመልክተዋል፡፡

ወይዘሮ ኤለማ ጀልዴሳ፣ የቦረና ዞን ዱብሉቅ ወረዳ፣ ላፍቶ ቀበሌ ማኅበር ነዋሪ ናት። የአምስት ልጆች እናት እንደኾነች የምትናገረው ወይዘሮ ኤለማ፣ ድርቁ ባዶ እጃቸውን ካስቀራቸው መካከል አንዷ ናት።

“ባለቤቴ እኔን ጨምሮ ሦስት ሚስቶች አሉት፡፡ ድርቁ ሳያራቁተን በፊት፣ ከበረት የምናሠማራቸው 50 የሚደርሱ ከብቶች ነበሩን፡፡ አሁን አንዲት ጥጃ እንኳን አልቀረችልንም፡፡ የእኛ ቤተሰብ፣ ከአማቻችንን ቤት ጋራ አራት ቤቶች አሉት፡፡ ከእኔ ብቻ አምስት ልጆች ተወልደዋል፡፡ የጣውንቶቼ ጨምሮ በአጠቃላይ ወደ ዐሥር ይኾናሉ። ከቤተሰባችን ሰው ቢታመም ወይም የኾነ እክል ቢገጥመው፣ የምንሰጠው ነገር የለንም፡፡ ይህ ፈጣሪ ያመጣው ነገር ነው።”

አቶ ገርብች ዳለቻም፣ በላፍቶ ቀበሌ ነዋሪ ሲኾኑ ፤ “ቀደም ሲል በባንክ የነበረኝን ተቀማጭ፣ ለከብቶቹ መኖ በመግዛት ነው የጨረስኹት፡፡ ኾኖም አሁን፣ ከ180 ከብቶች የቀሩኝ ሁለት ብቻ ናቸው፡፡ ከነበሩኝ ከ200 በላይ ፍየሎች፣ አሁን የተረፉት አምስት ብቻ ናቸው፡፡” ይላሉ።

አክለውም፤ “በጎቹ ደግሞ 150 ነበሩ፤ አሁን ያሉት ሰባቱ ብቻ ናቸው። ድርቁ ይህን ያህል ሀብት አውድሞብኛል፡፡ አብዛኞቹ ነዋሪዎችም፣ እንደ እኔ ያለ ጉዳት ነው የደረሰባቸው፡፡ ከእነርሱም፣ የቤት እንስሶቻቸው ያለቁባቸው ሰዎች አኀዝ ይበልጣል ባይ ነኝ። ምክንያቱም፣ በዚኽ በላፍቶ ቀበሌ ካሉት ከ600 በላይ አባወራዎች፣ አንድ ወይ ሁለት ከብት በእጃቸው የተረፈላቸው፣ ከ20 ወይ ከ30 ሰው አይበልጡም።” ብለዋል።

ቦረና ዞን፣ በተለይ በቀንድ ከብቶች የሚታወቅ የአርብቶ አደሩ አካባቢ ነው። በፊት በየአውራ መንገዱ የሚታዩት እንስሳት፣ በድርቁ በብዛት ስለ ሞቱ፣ በገጠሩ አካባቢ ሳይቀር የሚታየው የከብቶች ቁጥር በጣም አናሳ ነው።

ዶክተር ቃሲም ጉዮ፣ የቦረና ዞን የግብርና እና የእንስሳት ሀብት ልማት ጽሕፈት ቤት ምክትል ሓላፊ ናቸው።

“በቦረና ዞን ለአምስት የዝናም ወቅቶች ዝናም በመጥፋቱ፣ የሞቱት የቤት እንስሳት ቁጥር፣ ከ3ነጥብ3 ሚሊዮን በላይ ነው። ከ46 በመቶ በላይ የሚኾነው የዞኑ የእንስሳት ሀብት በድርቁ ጠፍቷል፡፡” ካሉ በኋላ “በቦረና፣ እንስሳት ግልጋሎት የሚሰጡት፥ ለምግብ እና ለምግብ ተዋጽኦ ብቻ አይደለም፡፡ የተለያዩ ባህላዊ በዓላት የሚከናወኑት በዚኹ ሀብት ነው፤ የክብርም ማሳያ ናቸው። ከዚኽ አኳያ፣ የድርቁ ጉዳት በነዋሪው ላይ የሚያደርሰው ተጽእኖ ቀላል አይኾንም።” ይላሉ።

አቶ ማልቸ ዳለቻ፣ የዱብሉቅ ወረዳ የእንስሳት ሀብት ጽሕፈት ቤት ባልደረባ፣ በተለይ በዚኽ አስከፊ ድርቅ፣ ክፉኛ ያለቁት ከብቶች እንደኾኑ ይናገራሉ።

“ድርቁን ተቋቁመው የተረፉት ከብቶች ከ20 በመቶ አይበልጡም፡፡ የዱብሉቅ ወረዳ፣ በከብት ሀብት፣ በቦረና ቀደም ከኾኑት አንዱ ነው፡፡ ባለፈው ዓመት፣ ከ150 ሺሕ በላይ ከብቶች ነበሩ፡፡ አሁን የተረፉት 34ሺሕ ቢኾኑ ነው። የእያንዳንዱ ነዋሪ ኢኮኖሚ እና የኅብረተሰቡ ባህላዊ ዕሤት፣ በእንስሳት ሀብት ላይ የተመረኮዘ ስለኾነ፣ ነዋሪው በጣም ተጎድቷል፡፡”

በቦረና ዞን በ“ቡሳ ጎኖፋ” የመረዳዳት ባህል መሠረት፣ እንስሶቻቸው ከእጃቸው ላለቁባቸው ነዋሪዎች በሙሉ እየተከፋፈሉ በመዳረስ ላይ ናቸው፡፡ ኾኖም፣ የተቀረው የእንስሳት ሀብት ውስን ስለኾነ፣ የመንግሥት እና የሌሎች ተቋማትን ድጋፍ እንደሚሹ ይናገራሉ። ለዚኽም፣ የዞኑ ግብርና እና እንስሳት ሀብት ጽሕፈት ቤት በሥራ ላይ መኾኑን፣ ዶክተር ቃሲም ገልጸዋል።

አንድ መቶ ከብት ለሞተበት ሰው፣ መቶዎቹንም እተካልኻለው ማለት አይቻልም፡፡ ይኹን እንጂ፣ የተወሰነ ከብት መተካት አስፈላጊ ስለኾነ፣ ይህን ከክልሉ መንግሥት ጋራ ኾነን እየሠራንበት ነው። ማኅበረሰቡን፣ ወደ ኑሮው እና ቦታው ለመመለስ የሚቻለው፣ በልገሳ ብቻ አይደለም፤ በማስተማርም ነው።

በሌላ በኩል፣ በቦረና፣ “ቦሳ ጎኖፋ” የሚባል የዳበረ የመረዳዳት ባህል አለ፡፡ አንድ ሰው አምስት ፍየሎች ካሉት፣ ለሌለው አንድ ወይ ሁለት በመስጠት፣ ወዳጁን የሚያግዝበት አካሔድ ነው። በዚኽም ራሱ ኅብረተሰቡ፣ ከ200ሺሕ በላይ እንስሳት ከእጃቸው አልቀው ባዶ እጃቸውን ለቀሩት አርሶ አደሮች፣ እርስ በራሱ በመረዳዳት ላይ ነው። መንግሥትም ይህን ዝም ብሎ አይመለከትም፡፡ እኛ ሰዎቹ የሚረዱበትን አካሔድ ለማሳለጥ፣ የርዳታ ምክረ ሐሳቡን ሠርተን ለክልሉ ሓላፊዎች አድርሰናል፤ ምላሽም እየተጠባበቅን ነን። ዶክተር ቃሲም፣ ዞኑ፥ የሣር ምርት መጀመሩን ገልጸው፣ ከብቶችን አርብቶ ከማደር በተጨማሪ፣ ሌሎች የኑሮ ዘይቤዎችን የማበረታቱ ሥራ መቀጠል እንዳለበት አሳስበዋል።

ተጨማሪ ይጫኑ

XS
SM
MD
LG